በመንግስትና በልማት አጋሮች ትብብር በሚቀጥሉት ሶስት ወራት በጋራ በሚከናወኑ ተግባራት ላይ የምክክር መድረክ ተካሄደ፡፡
Nov. 25, 2022
ህዳር 16 / 2015 ዓ.ም - በመንግስትና በአለም አቀፍ የልማት አጋሮች ትብብር በኢኮኖሚ፣ በማህበራዊና በመልሶ ማቋቋም ጉዳዮች ላይ በሚቀጥሉት ሶስት ወራት ውስጥ በሚከናወኑ ተግባራት ላይ በገንዘብ ሚኒስቴር መሰብሰቢያ አዳራሽ የምክክር መድረክ ተካሂደ፡፡
የምክክር መድረኩን የመሩት የገንዘብ ሚኒስቴር የኢኮኖሚ ትብብር ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ ክብርት ወ/ሮ ሰመሪታ ሰዋሰው እንደገለጹት መንግስት ከአለም አቀፍ የልማት አጋሮች ጋር በኢኮኖሚ፣ በማህበራዊ፣ በመልሶ ማቋቋምና በሌሎችም የልማት ጉዳዮች ላይ በጋራ ተጠቃሚነት መንፈስ ተቀራርቦ ለመስራት ቁርጠኛ መሆኑን አመልክተው ለወደፊቱም መንግስት ይህን ዘርፈ ብዙ ትብብር አጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል፡፡
በኢትዮጵያ መንግስትና በአለም አቀፍ የልማት አጋሮች ትብብር በሚቀጥሉት ሶስት ወራት ውስጥ በጋር የሚከናወኑት ዝረዝር ተግባራት የድርጊት መርሀግብር በልማት አጋሮች ቡድን ምክትል ሊቀመንበርና አማካሪ በዶ/ር ፒተር ሚድልብሩክ ቀርቦ አስተያየትና የማጠናከሪያ ሀሳብ ቀርቦበት እንዲጎለብት ተደርጓል፡፡
በምክክር መድረኩ ላይ የተገኙት የአለም አቀፍ የልማት አጋር ድርጅቶች ሀላፊዎችና ተወካዮች የኢትዮጵያን ልማት ለመደገፍ የተቋቋመው የልማት አጋሮች ቡድን የኢትዮጵያ ዘላቂ የልማት አጋር መሆኑንን አመለክተው ኢትዮጵያ በኢኮኖሚና በማህበራዊ ዘርፍ ውጤታማ ለመሆን የምታደርገውን ጥረት እንደሚደግፉ አረጋግጠዋል፡፡