የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ በአስቸጋሪ ወቅትም በውጤታማነቱ መዝለቁ ተገለጸ

March 3, 2022

የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ የስድስት ወር የስራ አፈፃፀም በገንዘብ ሚኒስቴርና በመንግስት የልማት ድርጅቶች ይዞታና አስተዳደር ዛሬ የካቲት 22 2014 ዓ.ም በሂልተን ሆቴል በተገመገመበት ወቅት የድርጅቱ ምክትል ዋና ስራ አሰፈፃሚ አቶ ኢሳያስ ወልደ ማሪያም እንዳስታወቁት ድርጅቱ ከመሰል ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ ድርጅቶች አንጻር በተለያዩ መመዘኛዎች ሲታይ የላቅ ዕድገት አሳይቷል፤ ትርፋነቱም በዚህ አስቸጋሪ ወቅትም ቀጥሏል ብለዋል፡፡

ምክትል ዋና ስራ አሰፈጻሚው አቶ ኢሳያስ ወልደ ማሪያም እንደገለጹት በግማሽ ዓመቱ ድርጅቱ 4 ነጥብ 1 ሚለየን ደንበኞችን ያጓጓዘ ሲሆን ይህም የእቅዱ 76 በመቶ ሲሆን ካለፈው አመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር ደግሞ የ73 በመቶ ብልጫ እንዳለው አስረድተዋል፡፡

አቶ ኢሳያስ እንዳስታወቁት ተቋሙ የወጪ ቅነሳ አሰራርን ተግባራዊ በማድረጉ ባለፉት ስድስት ወራት 608 ሚሊዮን ዶላር ከወጪ ያዳነ ሲሆን በሚሰጠው የተቀናጀ አገልግሎትም የደንበኞቹ እርካታ 72 በመቶ መድረሱንም ጨምረው ገልጸዋል፡፡

የግምገማ መድረኩን የመሩት የገንዘብ ሚኒስቴር ሚንስትር ክቡር አቶ አህመድ ሺዴ በአሁኑ ጊዜ በርካታ የአየር መንገዶች በአስቸጋሪ ወቅት ላይ ቢሆኑም የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ባሳየው ትረፋማነትና በወጪ ቅነሳ ረገድ ውጤት ማስመዝገቡ የሚደነቅ መሆኑን ጠቅሰው አየር መንገዱ በተለይ በዕቃ ማጓጓዝ አገልግሎት የሳየውን አመርቂ አፈፃፀም አጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት አሳስበዋል፡፡

ክቡር ሚኒስትሩ አየር መንገዱ አሁንም በወጭ ቅነሳ በኩል ብዙ መስራት እነደሚጠበቅበት ጠቁመው በተለይ በክልል ደረጃ የተጓተቱ ፕሮጅክቶች ላይ ትኩረት መስጠት እንዳለበትና የደንበኞች ዕርካታን በማሻሻልም ብዙ ስራ መስራት እንዳለበትም አመልክተዋል፡፡

842 Views