የገንዘብ ሚኒስቴር የትንሳኤ በዓልን ምክንያት በማድረግ ማእድ አጋራ
Published: April 9, 2026
ሚያዚያ 1/ 2018 ዓ.ም- የገንዘብ ሚኒስቴር የትንሳኤ በዓልን ምክንያት በማድረግ፣ አነስተኛ ደመወዝ ለሚከፈላቸው የተቋሙ ሰራተኞችና በአቅራቢያው ለሚገኙ ነዋሪዎች ማእድ አጋራ።
የገንዘብ ሚኒስትር ክቡር አቶ አህመድ ሺዴ በመርሀ ግብሩ ላይ እንደገለጹት ሚኒስቴር መ/ቤቱ የዚህ አይነቱን ድጋፍ በዋና ዋና በአላት ወቅት የሚያከናውን መሆኑን አመልክተው እንደ አገር ባህል እየሆነ የመጣውንና በክቡር ጠቅላይ ሚኒስትራችን የተጀመረ በጎ ተግባር እንደሆነን አላማውም ከተቋሙ ሠራተኞች እና በከአካባቢው ከሚገኙት የማኅበረሰብ አካላት ጋር ያለውን የመልካም ግንኙነት፣ የፍቅር እና የመረዳዳት እሴቶችን ለማጠናከር እንደሚያግዝ አስረድተዋል።
በሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ቅጥር ግቢ ውስጥ በተከናወነው በዚህ የማእድ ማጋራት ፕሮግራም ላይ አነስተኛ ደመወዝ ለሚከፈላቸው ለ265 የገንዘብ ሚኒስቴር ሰራተኞች ለእያንዳንዳቸው 10 ኪሎ ግራም ዱቄት፣ 5 ሊትር የምግብ ዘይት እና ለዶሮና ለእንቁላል መግዣ የሚሆን የገንዘብ ድጋፍ ተደርጎላቸዋል።
በተመሳሳይም በአራዳ ክፍለ ከተማ ወረዳ 6 ውስጥ ነዋሪ ለሆኑና ዝቅተኛ ገቢ ላላቸው ለ50 የህብረተሰብ ክፍሎች ለእያንዳንዳቸው የ10 ኪሎ ግራም ዱቄት እና የ5 ሊትር ዘይት ድጋፍ ተበርክቶላቸዋል።
ይህ ድጋፍ፣ ተቋሙ ካለው ማህበራዊ ኃላፊነት በተጨማሪ የመረዳዳትን እና የመተሳሰብ ባህልን ለማጎልበት ታስቦ የተዘጋጀ እንደሆነ ተገልጿል።
በማእድ ማጋራት መርሀ ግብሩ ላይ የገንዘብ ሚኒስትር ዴኤታ ክቡር አቶ ፍቃዱ ሆሮታን ጨምሮ ሌሎች የመስሪያ ቤቱ ከፍተኛ አመራሮችና ሰራተኞች ተገኝተዋል