የፀረ ጾታዊ ጥቃት (የነጭ ሪቫን) ቀን በገንዘብ ሚኒስቴር እና በተጠሪ ተቋማት ተከበረ
Dec. 8, 2021
በአለም አቀፍ ደረጃ ለ30ኛ ጊዜ በኢትዮጵያ ደግሞ ለ16ኛ ጊዜ “ሠላም ይስፈን በሴቶች እና ህጻናት ላይ የሚደርስ ጥቃት ይቁም!” በሚል መሪ ቃል የሚከበረው የጸረ- ጾታዊ ጥቃት ቀን ዛሬ ኅዳር 29 2014 ዓ.ም በገንዘብ ሚኒሰቴር እና ተጠሪ ተቋማት ሠራተኞች በጋራ ተከብሮ ውሏል፡፡
የፀረ-ጾታዊ ጥቃት ቀን በተከበረበት ወቅት ከግንዛቤ ማስጨበጫ መድረክ ጎን ለጎን ‹‹ደማችንን ለሀገር መከላከያ ሰራዊታችን›› በሚል መሪ ቃል ደም የመለገስ መርሃ ግብር ተከናውኖ 31 ሰራተኞች የደም ልገሳ አድርገዋል፡፡
በአለም አቀፍ ደረጃ ቀኑ መከበር የጀመረው እ.አ.አ በዲሲምበር1993 ሲሆን የፀረ-ጾታዊ ጥቃት ቀን የሚከበረብት አላማ በሴቶች ላይ የሚፈጸም ማንኛውም አይነት አካላዊ ፣ስነ ልቦናዊ እና ኢኮኖሚያዊ ጉዳት የሚያስከትል ጾታን መሰረት ያደረገ የሀይል ጥቃትን ለመቃወም ነው፡፡
በገንዘብ ሚኒስቴር የመሰብሰቢያ አዳራሽ በተካሄደው መርሃ ግብር ላይ ከሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን፣ከህግ ባለሙያ ሴቶች ማህበር እንዲሁም ከሴቶች እና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር የተውጣጡ ባለሙያዎች በርእሰ ጉዳዩ ላይ ግንዛቤ የሚያስጨብጥ ጥናታዊ ጽሁፍ አቅርበዋል፡፡